በሀገራችን ካለው የኮቪድ 19 ስርጭት ጋራ በተያያዘ የተሰሩት የፈጠራ ፕሮፖዛሎች ዛሬ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በውድድሩ አጠቃላይ ከተመዘገቡት ውስጥ በሶስት የማጣርያ ዙሮች ተጣርተው ያለፉ 30 ፈጠራዎች ዝርዝር ውድድሩ የሚያስተናበረው የብሄራዊ የኢኖቬሽን ግብረ ኃይል አስተባባሪ የሆኑት አቶ አዲሱ ማሞ አማካኝነት ቀርቧል፡፡
በውይይቱ ጅማሮ የስራውን የእስካሁን ሂደት አስመልክቶ የቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክረተርና የዚህ ግብረ ኃይል መሪው አቶ ሙሉቀን ቀሬ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡
በሪፖርታቸውም 446 የፕሮጀክት ፕሮፖዛሎች መቅረባቸውን ገልፀው ከነዚህም ውስጥ 43 በመቶው ለምርት የተዘጋጁ፣ 31 በመቶው የተለያዩ የማበልፀጊያ ስራዎችን የሚሹ ሰርቶ ማሳያዎች እንዲሁም 26 በመቶው በሀሳብ ደረጃ ያሉ መሆናቸውን አስቀምጠዋል፡፡ ከፈጠራዎቹ ግማሽ ያህሉም የሶፍትዌር እና የሞባይል መተግበሪያዎች መሆናው እንዲሁም በአጠቃላይ ከተመዘገቡት ውስጥም በአንፃራዊነት ጥቂቶቹ የተሸለ ሀሳብ ይዘው መምጣታቸው በሪፖርታቸው ተካቷል፡፡
ፈጠራዎቹ የመተንፈሻ ማሽኖች፣ የእጅ መታጠቢያ፣ የሶፍትዌር ስራዎችን ጨምሮ በስድስት የተለያ ዘርፎች ተከፋፍለው ነው የቀረቡት፡፡ ከቀረቡት ስራዎች መካከልም የእጅ መታጠቢያ ላይ ያተኮሩ ፈጠራዎች፣ ካሉበት በመሆን ትምህረትን መከታተል የሚያስችል የስልክ መተግበሪያ ስርዓት፣ የኮቪድ-19 መከታተያ ስርዓት እና ሌሎች ምርቶችም ይገኙበታል፡፡
ዛሬ በቀረቡት ስራዎች ላይ በተሰበሰቡት ታዳሚያን በተለይ በሚሰጠው የድጋፍ አይነት እና ለየትኞቹ ፈጠራዎች ድጋፍ መደረግ እንዳለበት ከተሳታፊው ጥያቄና አስተያየቶች ተነስተው በአቶ አዲሱ እና አቶ ሙሉቀን አማካኝነት ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
የፈጠራ ስራዎቹን የሚገመግመው ከቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ኢኖቬተርስ አሶሴሽን፣ የኢትዮጵያ ባዮቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ የተውጣጡ 25 ባለሙያዎች ያሉት ቴክኒክ ቡድን ነው፡፡